Friday, April 11, 2014

ጋዜጠኝነት ለኢትዮጵያ ኢትዮጵያም ለጋዜጠኝነት የማትመች አገር



….ጋዜጠኝነት ለኢትዮጵያ ኢትዮጵያም ለጋዜጠኝነት የማትመች አገር መስላለች፡፡ ብእርን የጨበጡ፣ በሀሳባቸው ብልጫ ውድድሩን ለማሸነፍ የጣሩ፣ ሀሳባቸውን በጽሁፍ ሆነ በንግገር መግለጣቸው እንደነውር ተቆጥሮ ዶክመንተሪ የሚሰራባት፡፡ ሰብዓዊ መብት፣ፍትህ፣እኩልነት እነደማዕድን ተቆፍሮ እንኳን የማይገኝባት ሀገር ሆናለች ኢትዮጵያ፡፡
….ዲሞክራሲ እንደ ሰማይ የራቃት፣ ችጋር ስጋዋን አልፎ አጥንቷን መብላት የጀመረባት፤ ለለውጥ የተነሱ አብረን ተባብረን ወደ ፊት እንራመድ ያሉ እንደ አረም እየተመነጠሩ የሚታሰሩባት ሀገረ መከራ ሆናለች ኢትዮጵያ፡፡
….አንድነቷ ተጎንጉኖ የዘር እራቁትነት የለበሰች፣ ነገ እርስ በእርስ እንዳንበላላ የምታሰጋ፣ ጎጠኝነት እራቁቷን ያስቀራት፣ ኢትዮጵያዊ ነኝ የሚል ትምክህተኛ ሆኖ የሚፈረጅባት የመከራን ቁልቁል የምትጋልብ ሀገር ሆናለች ኢትዮጵያ፡፡
….ብሄራዊ መግባባት የጠፋባት፣ ሌላውን ላለማስገባት ሁሉም በሩን የዘጋበት፣ የሀገር ትርጉም የጠፋባት፤ ስለ ሀገር ሲጠየቅ ‹‹ምን አገባኝ›› የሚልን ተረት ተናጋሪ የበዛባት ሀገር ሆናለች ኢትዮጵያ፡፡
….ተቃዋሚ ፓርቲዎች ከራሳቸው ጋር መታረቅ አቅቶቸው አብሮቸው እየሮጠ ያለውን ጠልፈው የሚጥሉባት፣ ተገረፍን ታሰርን እያሉ በሰበብ አስባቡ አገር የሚለቁባት፡፡ ከዚህም የተነሳ ለውጥ ፈላጊው ህዝብ የተቃውሚ ፓርቲዎችን ጭመር በጥርጣሬ የሚያይባት፡፡ ለተቃዋሚም ለመሪም ያልታደለች፣ የመንግስት ለውጥ እንጂ እውነተኛ ለውጥ ያልሰመረላት አገር ኢትዮጵያ፡፡
…..ዛሬም ልጆቿ ይታሰራሉ፣ያለከልካይ ከቦታቸው ይፈናቀላሉ፣ ይደበደባሉ አካላቸው ይጎላል፡፡ሙስና የመጨባበጥ ያህል የቀለለባት፣ከደሀ 10 ካ.ሜ ተነጥቆ ለባለ ገንዘብ 10,000 ካ.ሜ የሚሰጥባት፡፡ ዜግነት በገንዘብ እና በአሸርጋጅነት (በተለጣፊነት) የሚከበርባት ሆናለች ሀገሬ ኢትዮጵያ፡፡
…..የሀይማኖት መሪዎች ‹‹እ/ር የእውነት አምላክ ነው፡፡ ሀሰትም በሱ ዘንድ የለም፡፡›› የሚለውን ሰርዘው በሀይማኖት ካባቸው ስር ሀሰትን ያቀላጥፋሉ፡፡ አደግን፣ ሄድን፣ ደርሰናል እያሉ የምድር ጥቅማቸውን ተምነው ይመላለሳሉ፡፡ አረ እንደውም እ/ር ነጻነታችንን ሰጠን እያሉ በየድንኳኑ የሚጮሁም አሉ፡፡ ማን ነበር ልማታዊ ፓስተር ነኝ ያለው??
‹‹እኛ የሰማይ ቤት አለን የምድሩ የእኛ ስላልሆነ እኛን አይመለከተንም›› የሚሉ ፖለቲካ ለሀጢያን የተተወ ስራ እንደሆነ የሚቆጥሩ ምእመናን እና አስተማሪዎች የተበራከቱባት ሆናለች አገራችን ኢትዮጵያ፡፡
ሙሁሮቿ የት ጠፉ???
ውስጣችን የተፈጠረው ዘረኝነት ከየት መጣ???
ዛሬም ከአለም የታችኛው ተርታ ለምን ተሰለፍን???
የተማረና ያለተማረ ሰው መሀል ያለው የኑሮ ልዩነትስ ምን ያህል ነው???
ኢትዮጵያዊ ሆነን ተፈጥረን፤ የታል ታዲያ ኢትዮጵያ ለኛ የሆነችው??? ችግር፣ረሀብ፣ፍርሀት… ከተፈጠሩባት ሀገራቸው አሰድዶአቸው በሀገር ናፍቆት ሌላ አገር ላይ የሚኖሩ ስንቶች ናቸው??
እውነት እውነቱን ብናወራ በዚህ አካሄዳችን የአትዮጵያ የወደፊት ተስፋ ብሩህ ነውን???
እነዚህ ጥያቄዎች እንደ ማለዳ አንቂ አላርሞች ዙሪያችን ላይ በእየለቱ ይጮሀሉ፤፤
ጉዳዩ አሁን እንደ ጣውንት የቆመውን ስርአት መቀየር ብቻ አይደለም፡፡ የራሳችንንም የአስተሳሰብና የአመለካከት ደጅ መቀየር ያለብን ይመስለኛል፡፡
By Robel Ayalew

No comments:

Post a Comment